Sunday 13 August 2017

ለምን ጎንደርን? (ሰሜን ጎንደርን ለ 3 ዞን መሰነጣጠቅ ያስፈለገበት ፓለቲካዊ ምስጥር)

(በደርብ ተፈራ)

እርስ በርስ ህዝብን በማጋጨትና አንዱ ከሌላው እንዳይግባባ በተለያየ ፓለቲካዊ ሴራ መከፋፈል የለመደው አገዛዝ ጎንደር ላይ ተጨማሪ ሰይጣናዊ ስራውን ሊፈፅም ዝግጅቱን አጠናቋል፡፡

ሰሞኑን ሪፓርተር ጋዜጣ እንደዘገበው ሰሜን ጎንደር ለ3 ትንንሽ ዞኖች ሊሰነጣጠቅ ነው፡፡ 16 ወረዳዎችን ያቀፈው ሰ/ጎንደር ዞን ዛሬ ላይ ትልቅ አደጋ ተጋርጦበታል፡፡ ይህ ዞን እንደ CSA (2007) መረጃ ከሆነ  2,929,628 የሚደርስ ህዝብ በስሩ ያቀፈ ነው፡፡ ዞኑ የመሰረተ ልማት እጦት እንዳለበት ነዋሪዎች ቅሬታቸውን ሲገልፁ እንደነበር ይታወሳል፡፡ የአለም ባንክ በወርሃ ግንቦት 2004 ላይ ባወጣው መረጃ መሰረት በዞኑ የነበረው የኤሌክትሪክ አቅርቦት ከ 7% ነዋሪዎች በስተቀር  ቀሪውን ማዳረስ ያልቻለ ነበር፡፡ ይህን መሰል ችግሮች እያሉ የህዝቡን የልማትና ፍትህ ጥያቄ ችላ ያለ መንግስት ለመከፋፈል ሲሆን ግን ሌት ተቀን ይሰራል፡፡
በከፋፍለህ ግዛ ስልት የተካነው ኢህአዴግ የማንነት ጥያቄ ሲነሳ አማራ ክልልን የሚከፋፍል ከሆነ በደስታ ይቀበላል፡፡ ካልሆነ ግን ጆሮ ዳባ ልበስ ይላል፡፡ ለዚህ ማሳያ ቅማንት ላይ የሰሩትን ማየት በቂ ነው፡፡ የፌደሬሽን ም/ቤት ያመነበት እንኳ አምስት (5) ማህበረሰቦች የማንነት ጥያቄ አቅርበው ጉዳያቸው እልባት አላገኘም፡፡ የቅማንትን ጉዳይ ግን ጎንደርን ለመከፋፈል ስለሚጠቅም አራገቡት፡፡ ተሳካላቸውም የቅማንት ህዝብ የራሱ አስተዳደር ሊሰጠው እንደሆነም ታውቋል፡፡

 የማንነት እና የራስ ገዝ አስተዳደር ጥያቄዎች ሲነሱ በድብቅ ሲያፍን፣ ሲገድ፣ ሲያስር እና የዜጎችን ሰብዓዊ መብት ሲረግጥ የነበረ መንግስት በራሱ ጉልበት ጎንደርን ለማዳከም በዞን ሲሰነጣጥቅ ማየት ያሳዝናል፡፡ በቁጫ እና ኮንቶማ ማህበረሰቦች ላይ ጥያቄ ባነሱ በምላሹ ምን እንደተደረገ የምናቀው ጉዳይ ነው፡፡

በያዝነው አመት ግንቦት ወር ላይ የፌዴሬሽን ምክር ቤት በአፋር ክልል አብዓላ ወረዳ የሚኖሩ የትግራይ ብሔር ተወላጆች ያቀረቡትን የልዩ ወረዳ ጥያቄ ውድቅ ማድረጉን ሰምተናል፡፡ ነዋሪዎቹ  “የማንነት መብታችን ቢከበርም ራስን በራስ የማስተዳደር መብታችን ተሸራርፏል” የሚል ቅሬታ ለክልሉ አቅርበው ነበር። ከዚህ በተጨማሪ ተወላጆቹ “ቋንቋችን፣ ባህላችንና ታሪካችንን የምናሳድግበት ሁኔታ አልተመቻቸልንም” በማለት ጥያቄ እንዳቀረቡም ተመልክቷል። የአፋር ብሔራዊ ክልላዊ መንግስትም ጉዳዩን አጥንቶ አመልካቾቹ “ራሳቸውን በራሳቸው የማስተዳደር መብት የሌላቸው በመሆኑ ያቀረቡትን ጥያቄ ውድቅ አድርጎ ነበር” ተብሏል በወቅቱ በሰማነው ዘገባ፡፡ ይህን ጉደይ ያነሳሁት ምን ያክል ሌሎች ክልሎች ከአማራ ክልል የተሻለ የመወሰን ስልጣን እንዳላቸው ነው፡፡ አማራ ክልል ሲሆን የፌደራል መንግስት ጣልቃ ገብቶ ይፈተፍታል፡፡ እዚህ ላይ የማንነት ጥያቄ የተመለከተ ሀሳብ የተነሳው የመንግስትን ውሳኔ ለመታዘብ እንጅ ከጎንደሩ እውነታ ጋር የተገናኘ ስለሆነ አይደለም፡፡ የጎንደሩ አንድን ህዝብ በዞን ከፋፍሎ ማዳከም ነው፡፡

እስኪ ከዚህ የፓለቲካ ሴራ በስተጀርባ ካሉት አነሳሽ ምክንያቶች መካከል የተወሰኑትን እንይ፦

ሀ. ጎንደር አካባቢ የተነሳው የተቃውሞ ትግል ላይ ቀዝቃዛ ውኃ ለመቸለስ

መንግስት ከወደ ጎንደር ከፍተኛ የሆነ ተቃውሞ እየገጠመው ስለተቸገረ ጎንደርን በመንደር አስተሳሰብ አስሮ ትንሽ ፋታ ለማግኘት ያሰብ ይመስላል፡፡ ሰ/ ጎንደር በዞን መሰነጣጠቁ እርስ በርስ የጥቅም ግጭት እንድነሳ እና የጎንደሬነት ስሜት እንድቀዘቅዝ ማድረጉ አይቀርም፡፡ ይህ ደግሞ ለመንግስት በለስ የቀናው ያክል ነው፡፡

ለ. አማራን በተለያየ ዘዴ ለማዳከም

ገለን ቀብረነዋል ያሉት አማራ መቃብር ፈንቅሎ የወጣ ስለመሰላቸው በቻሉት መጠን ከፋፍለው እየቅል መምታት ይፈልጋሉ፡፡ ለዚህ ደግሞ የጎንደሩ አይነት ሴራ ተቀዳሚ አማራጭ ነው፡፡ ቢቻላቸው አማራ የሚባል ህዝብ ከምድረ ገጥ ቢጠፋ ይደሰታሉ፡፡ ይህ ባይሳካ ደግሞ እርስ በርሱ ማናከሱ ቀሪ አማራጭ ነው፡፡ ገና ብዙ ነገር እናያለን፡፡ ተንኮላቸው ገደብ የለውም፡፡

ሐ. በመልካም አስተዳደር ስበብ ህዝብን ማታለል

ሰ/ጎንደር ብዙ ህዝብ የሚኖርበት ዞን ስለሆነ ለአገልግሎት አሰጣጥ አይመችም የሚል ስንኩል ምክንያት እያቀረቡ እንደሆነ በሰማን ጊዜ ተገርመናል፡፡ ይህ ከሆነ ለምን ደቡብ ክልል የሚነሱ መሰል ጥያቄዎችን አይመልሱም፡፡ ለምን ጎንደርን? የመልካም አስተዳደሩ ችግር ለጎንደር ህዝብ ያላቸው ጥላቻ መገለጫ እንጅ የህዝብ ብዛቱ ያመጣው አይደለም፡፡ ወረዳዎች የተዋቀሩት ለተመሳሳይ አላማ አልነበረምዴ? በዞን መሰነጣጠቁ ምን የተለየ መፍትሄ ይዞ ሊመጣ? በመልካም አስተዳደር ሰበብ የሚደረገው ሴራ ተቀባይነት የለውም፡፡

ጎንደር ላይ የታቀደው ሴራ በክልሉ ም/ቤት ከፀደቀ ጎንደር አደጋ ላይ ወደቀች፡፡ በዞን የመሰነጣጠቁ ሀሳብ በክልሉ ካቢኔዎች ሙሉ ድጋፍ ያገኘ እንደሆነ ሪፓርተር መዘገቡ ይታወሳል፡፡ አሁን የቀረው የክልል ም/ቤት ውሳኔ ብቻ ነው፡፡ መንግስት ያላወቀው ነገር  ጎንደር በዚህ እና መሰል ተንኮል ተስፋ እንደማይቆርጥ ነው፡፡


No comments:

Post a Comment

የፖለቲካ ባህላችን

አየሽ እዚህ አገር ከንቱ ፍረጃ አለ፤ አማኝ ሁሉ አክራሪ፤ ሙስሊሙ አሸባሪ፤ ጉራጌ ቋጣሪ፡፡ ትግሬ ሁሉ ወያኔ፤ ወጣቱ ወመኔ፡፡ አማራው ነፍጠኛ ፤ ደርግ ሁሉ ግፈኛ፡፡ ናቸው እያስባለ ፤ ቁልቁል የሚነዳን ጭ...